ቫንኩቨር፡ ብርቱካን ሚደቅሳ የታሰረችበትን አንደኛ አመት አከበረች
በቫንኩቨር የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን፡ በታህሳስ 20 2001 ዓ.ም. በወያኔ ወታደሮች ያለአግባብ ተይዛ ቃሊቲ እስር ቤት የተወረወረችውን የአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ መሪ፡ ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ የታሰረችበትን አንደኛ ዓመት አክብረው ዋሉ። እንደፈረንጆቹ አቆጣጠር፡ ቅዳሜ ታህሳስ 27፡ ከቀኑ አራት ሰዓት እስከ 7 ተኩል ሰዓት በተካሄደው በዚሁ ስብሰባ ላይ ብዛት ያላቸው ኢትዮጵያዊያን የተገኙ ሲሆን፡ ነዋሪነታቸው በሲያትል የሆነውና የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ፕሮፌሽናል የካርታ ስራ ባለሙያ፡ አቶ ዘውገ ፈንታ ንግግር አቅርበዋል።
አቶ ዘውገ ፈንታ፡ ብርቱካን አንደኛ እውቅናን እያገኘች በመምጣቷ፡ ሁለተኛ አቶ መለስ ዜናዊ ለኢትዮጵያ ህዝብ ንቀት ስላላቸውና ህዝቡን ለማስፈራራት፡ ሲሉ እንደታሰረች ተናግረዋል። የብርቱካን እስራትም የኢትዮጵያን ህዝብ እስራት እንደሚያሳይ ጨምረው ተናግረዋል። አቶ ዘውገ አስከትለውም፡ ሰው ለማሸነፍ የግድ ይታሰር ማለት ባይቻልምና ወያኔ ብርቱካንን ያሰራት ሞራሏን ለመስበርና ለመርታት ቢሆንም፡ ብርቱካን ግን ከእያንዳንዱ በእስር ቤት ከምታሳልፈው ሴኮንድ፤ በኢትዮጵያዊያን ዘንድ፡ ያስር ዓመት ክብር እንደምታገኝ ተናግረዋል።
አቶ ዘውገ በተጨማሪም፡ በኢትዮጵያ ውስጥ ያለው አፋኝ ስርአት፡ ጸረ-ኢትዮጵያ ከመሆኑ የተነሳ፡ የኢትዮያን ድንበር ለሌሎች አገሮች አሳልፎ እየሰጠ መሆኑን ተናግረዋል። የመጀመሪያውን ባለቀለም የኢትዮጵያንና የአዲስ አበባን ካርታ የሰሩትና፡ በልጅነታቸው ላገራቸው ባበረከቱት ከካርታ ጋር የተገናኘ ስራ በጃንሆይ ዘንድ ቀርበው የተሸለሙት፤ በኋላም የትምህርት እድል አግኝተው ወደአሜሪካን የመጡት አቶ ዘውገ ፈንታ፡ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ፤ በወያኔ ለሱዳን አሳልፎ የተሰጠውን በሰሜን ምእራብ ከተሰነይ እስከ በጎንደር ሁመራ አልፎ እስከ ኦሜድላ የሚደርስ መሬት ተዘዋውረው እንዳጠኑና ካርታውንም እንደሰሩ፡ የወያኔው መሪ አቶ መለስ ባንድ በኩል ኢትዮጵያ ምንም መሬት ለሱዳን አልሰጠችም ብለው በሌላ ቀን ደግሞ ከሱዳን የወሰድነውን መሬት መልሰን ሰጥተናል ማለታቸው ርስ በርሱ የሚቃረን መሆኑን ጠቁመዋል። አቶ ዘውገ በተጨማሪም፡ ኢትዮጵያ አሁን የምትመራበት ቋንቋን መሰረት ያደረገ ፌደራሊዝም ለኢትዮጵያ የማይበጅና ከፋፋይ መሆኑን ጠቁመው፡ እሳቸው ለኢትዮጵያ ይበጃል ስለሚሉት የመሬት አቀማመጥንና ታሪክን መሰረት ያደረገ የአስደዳደር አወቃቀር ተናገርዋል።
ከአቶ ዘውገ ንግግር በተጨማሪም፡ በብርቱካንና በድንበር ጉዳይ ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጐ፡ የእለቱን ዋና ጉዳይ የብርቱካንን መታሰር መሰረት ያደረገ የገንዘብ ማሰባሰቢያ ዝግጅተም ተደርጓል። በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ በሰፊው በመንቀሳቀስ የሚታወቁት አቶ ከበደ ሀይለማሪያም፡ የብርቱካንና የልጇ ምስል ያለባቸውን የቡናና ሻይ ኩባያዎች አቅርበው፡ ሁሉም ተቸብችበው ገቢው ለብርቱካን ሚደቅሳ ቤተሰቦች እንዲላክ ሰጥተዋል። በእለቱ አንዳንድ ኢትዮጵያዊያን የኢትዮጵያን ህዝብ መንገፍገፍ የሚጠቁሙ አልባሳትን ለብሰው ተስተውለዋል። ከኢትዮጵያ ተሰደው ነዋሪነታቸው በካናዳ የሆነው ወ/ት አለምጸሀይ ዳምጤ “በቃ” የሚውን ካኒቴራ ለብሰው የኢትዮጵያ ህዝብ በወያኔ/ኢህአዴግ አገዛዝ ምን ያህል እንደተንገፈገፈ ተናግረዋል።
ነጻ ተመልካችና ዘጋቢ፡ ከቫንኩቨር፡ ታህሳስ 27፡ 2009 ዓ.ም.



December 27th, 2009 at 18:27 | #4 ይመልሱ | ይጥቀሱ ))))))))))ደጋግሞ መታለል።((((((((((((
እሳቸው”ክርስቲያን ተስፋ አይቆርጥም”ሲሉ ፤አጠገባቸው የቆሙት ደግሞ “እንዲሁም እስላም”አሉ ይባላል።ሁለቱም ኢትዮጵያውያን አባቶቻችን ያለምንም የሐይማኖት ልዩነት ያነሱት የምሳሌው ቁም-ነገር አይደለም።
ባንዳው-ወያኔ ደግሞ “እሺ ሕጉን ተከትላችሁ በሰላማዊ መንገድ ለምትጠይቁኝ ስህተቴን አርሜ የሕዝቡን ጥያቄ እመልሳለሁ”ካለ የአሥራ ስምንት አመታት ጊዜያት አለፉን።አንዴ መታለል፤አልፎም ሁለቴ መጭበርበር የሰው ልጅ ስህተት ነው፤ደጋግሞ መታለል ግን የጤና አይደለም እና በሽታ ነው።በትንሹ አሥራ ስምንት ጊዜ፤ መሞከር ሳይሆን መታለል ነውና የበሽታ ነው፤ድግግሙ።
ታዲያ ብርቱካንን በተመለከተ የመለስን አነጋገር ያደመጠ “እንደእሱው”አታላይነቱን “ከመጨረሻው የቃሉ ውሳኔ” እንረዳለን።በሰላም “ሠላም” የለም ማለቱን ለማዋጥ ነውና ዛሬም አንታለል።
ቢያንስ የሻማ ማብራቱን ስርዓት ለተወሰኑ ደቂቃዎች በሥርዓቱ ላይ ሻማዎቻችንን በማጥፋት የብርቱካንን የእስር ቤት የጨለማ ኑሮዋን በተለየ መልኩ ብናሳይ የበለጠ የሰቆቃ ሕይወቷን መጀመሪያ እኛው እናጣጥመዋለን።
ሌላው ሙከራ ደግሞ ፤ ተንቀሳቃሽ የጨለማ ቤት በየሻማ ማብራቱ ስርዓት ላይ ማሳየቱ በጅምሩ መበረታታት ይኖርበታል።በግድ ኢትዮጵያውያን ብቻ መሆን የሉባቸውም፤ጉዳዩ የሰብዓዊ መብትና የሕዝብ የፖለቲካ ነፃነት ነውና ሌሎቹም ዜጎች ይጋሩናል።የተቀናጀ ዝግጅት የሚባለውም እድገት እና ለውጥ ሲኖረው ነውና በርቱበት እላለሁ፤ለአዝጋጂዎች።
በሌላ በኩል እነመለስ ለምን ብርቱካንን እንደጦር ፈርተው “የመጨረሻ” ቃሉን መለስ ወስኖ ተናገረ???ምክንያቱም ባንዳ-ወያኔ የሕዝብ ወገን የሆኑትን የሚያጠምድበትና እንደመንጠቆ እየጎለጎለ፤በእባብ ተንኮሉ እየወታተበ እና በእስስት የውጭ ቅርፁ እየተለዋወጠ የሚያኮላሽበት የጭንብል ተንኮል “ሕግ”መሆኑን ብርቱካን ጠንቅቃ ስላወቀችና መቼም ቢሆን ከሙያዋ አንፃር ስለማይመጣጠኗት ነው። አለበለዚያ በቅድሚያ መቶ ሥልሳ ሺህ ዶላር ቀብድ ተከፍሏት ባገር ውስጥ ላሉትም ሆነ በውጭ አገር ለሚኖሩት ኢትዮጵያውያን “የባንዳ-ወያኔን” የዲሞክራሲያዊ
መንግሥትነት በተዘዋዋሪ መንገድ ድጋፏን መስጠት አይከለክላትም፤ሆኖም የዓላማ ፅናት አላትና የሕዝቡን ፍቅር አልሸጠችም።እንደውም ጀግና ነኝ ይል የነበረው ባንዳው-ወያኔ ምንም መሳሪያ
በሌላት ሴቷ ብርቱካን ሚደቅሳ ላይ ጠመንጃ ይዞ የፈሪነቱን መጨረሻነት በብረት አምልኮነቱ አረጋግጧል።ሁሉም ብረት ካለው ጀግና መሆን ይችላል፤ዛሬ ይህንን የማያውቅ ካለ በሽተኛ ብቻ ነው።
ታዲያ መቼ ነው የተቀናጀ የትግል ስልት የሚኖረን???አለበለዚያ ግን ደጋግሞ መታለል ነውና በዚሁ ድህረ-ገፅ ከአሥራ-አምስት አመታት በፊት በየጊዜው የፃፍኳቸውን ይመልከቱ።ይህ የባንዳ-ወያኔ መንግሥት ነኝ ባይ ደጋግሞ ከማታለል በስተቀር መቼም የማይለወጥ ዘረኛ ቡድን ነው።
1. January 10th, 2009 at 06:36 | #3
ይመልሱ | ይጥቀሱ
)))))))የዮዲትን ታሪክ አስታወሰኝ!!!(((((((
የድርጅቶቹ ጥረት የመጀመሪያው:እርምጃ ነው።ለፖለቲካ እስረኞች በሙሉ ቢጠይቁ ይመረጣልና ቀጣዩን እንቅስቃሴ ከመድኃኔዓለም እርዳታ ጋር እየጮህን እንጠብቃለን።
ብታምኑም ባታምኑም ስንትና ስንት የጦር ሙያ ያላቸው ሰዎች፣ጄኔራሎችን (አሁን ያሉትን ሹመኞች ሳይሆን)ጨምሮ የጙዋሮ አትክልታቸውን እያጠጡ፣በደህና ጊዜአቸው ያከማቹትን ንብረት እየተቆጣጠሩ መልካም እንቅልፋቸውን ከኢትዮጵያዊነት ዜግነታቸው ጋር ሞታቸውን ያባብላሉ።እናም ይህንን የአጋዚ መንግስት የወረቀት ላይ ነብሮች በልሳናቸው ብቻ ሊያሸንፉት ይችላሉ ብሎ ለማመን ያስቸግራል፤ሕዝብ አሸናፊ መሆኑን ባውቅም።
ብታምኑም ባታምኑም፣ ይህ ጥፋት የመጣው ከእግዚአብሔር ሰማያዊ ቅጣት ሲሆን የሚመለሰውም በእሱ ፈቃድ ብቻ ነው፤ማንም በማይገምተው ፤ይህንን የሰው ሰራሽ ሰቆቃ እርግማን ጨምሮ።
እናም፣መጀመሪያ ወያኔን የምትዘረጥጠው ደግሞ ሴት ብቻ ናት።ጉዳዩ የጀግንነት ሳይሆን የኢትዮጵያዊነት ታሪክ ነውና የዮዲት ጉዲትን ታሪክ ይመልከቱ።
ሌሎች ብዙ ብርቱካን ሚደቅሳዎች ደግሞ አስፈፃሚዎች ናቸው።ሐይማኖት፣ዘር፣ቆዳ፣አጥንት፣ደም፣ድንበር፣አይደለም መለያቸው ኢይዮጵያዊነት ብቻ ነው።
የኢትዮጵያ አምላክ ይጠብቃታል።
)))))))))))የብርቱካን፡እሳት!!!(((((((((((
ተንኮልን፡ያልጫረ፤
ደም፡ያልተነከረ።
ዕውቀት፡የቋጠረ፤
ለሰላም፡ያደረ።
ይፋጃል፡በጠዋት፤
የብርቱካን፡እሳት።
እሳት፡ነው፡የፋመ፤
ውስጥ፡ውስጡን፣
የጋመ።
በቀላል፡የማይነድ፤
በትዕግስት፡አመድ፤
ተዳፍኖ፡የረመጠ፤
ትግል፡እያማጠ፤
እያማጠ፡ፍቅር፤
ለኢትዮጵያ፡ሲያዘምር፤
ይፋጃል፡በጠዋት፤
የብርቱካን፡እሳት።
ገና፡ገና፤
ይለበልብና፤
አልነደደም፡ሲባል፤
ሐቅንም፡ያግታል።
ትናንትና፤
ቀን፡ተቆጠረና፤
በእድሜአቸው፡ቢጠሩ፤
እንዲመሥክሩ፤
ሽማግሌ፡ሆነው፡መናገሩን፡ፈሩ፤
ከነማተባቸው፡በየጓዳ፡ቀሩ።
ግና!!!!
ግፍ፡አይቀርምና።
ደም፡ያልተነከረው፤
ዕውቀት፡የቋጠረው።
ለሰላም፡ያደረው፤
አሳዶ፡ ‘ማይምረው።
ይፋጃል፡በጠዋት፤
የብርቱካን፡እሳት።
ሰማን፡ትናንትና፤
በድንገት፡ሆነና።
አመፁ፡በርክቶ፤
ፈነዳ፡መርካቶ።
ፈነዳ፡በዓለም፡ላይ፤
ሕዝብ፡ወጣ፡አደባባይ።
ለእነቴዲም፡ጮህን፤
ለእስረኞች፡በሙሉ፤
ሰሚ፡ጠፋ፡ግና፣
ይቀጥላል፡ትግሉ።
እናም!!!
ፈሰሰም፡አልፈሰሰም፤
በፍትሕ፡ዓለም፤
ደም!!!
ሙት፡አይደለም።
ዝግጁ፡ነው፡በግልፅ፣
ሰንጥቆ፡ለማጋት፤
ለብልቦ፡ያሳምናል፣
የብርቱካን፡እሳት!!!